ዓባይ ባንክ ከምሥረታው ጀምሮ በታማኝነት እና በትጋት ላገለገሉ ሠራተኞቹ ዕውቅና ሰጠ
ሠራተኞቹ ሁሉንም ተግዳሮቶች ተቋቁመው የዓባይ የታላቅነት ጉዞ ምሥክር መሆን በመቻላቸው ደስታቸውን ገልፀው፣ ለዚህም ዕውቅና መሠጠቱ የታማኝ አገልጋይነት ዕሳቤን ያሳድጋል ብለዋል።
የዓባይ ባንክ ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ የኋላ ገሠሠ ሠራተኞቹ ለ15 ዓመታት በባንኩ ውስጥ በማገልገላቸው ላቅ ያለ ምስጋና ያቀረቡ ሲሆን፣ ባንኩ ላስመዘገበው ሁለንተናዊ ዕድገት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ማበርከታቸውን ገልጸዋል።
በተጨማሪም ባንኩ የተመሠረተበትን 15ኛ ዓመት አከባበር አስመልክቶ ሲከናወኑ ከቆዩት በርካታ የኮርፖሬት ማኅበራዊ ኃላፊነት ውስጥ በድምቀት የደም ልገሳ መርሐ-ግብር አንዱ ነበር። በዚህ የባንኩ የሕይወት -አድን ተግባር ከፍተኛ አስተዋጽዖ ላበረከቱ ዲስትሪክቶች፣ ቅርንጫፎች እና ሠራተኞች የዕውቅና የምሥክር ወረቀት ከምስጋና ጋር ተበርክቶላቸዋል፡፡
ባንኩ ዕውቅናውን የሰጠው የ2025/26 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ግማሽ ዓመት የሥራ አፈፃፀሙን በአዲስ አበባ ኃይሌ ግራንድ ሆቴል በገመገመበት መድረክ ላይ ነው።
ዓባይ ባንክ ለሁለት ቀናት ያካሄደው የ2025/26 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ግማሽ ዓመት የሥራ አፈፃፀም ግምገማ አቶ የኋላ ገሠሠ በሰጡት ቀጣይ የሥራ አቅጣጫ ተጠናቅቋል፡፡
ሐምሌ 07 ቀን 2002 ዓ.ም የተመሰረተው ዓባይ ባንክ የታላቅነት ጉዞውን ዕውን እያደረገ ድፍን 15 ዓመታትን አስቆጥሯል።



ዓባይ -የታላቅነት ምንጭ!